የሕጻናት እድገት መሰላል
ስለ ሕጻናት እድገት ሂደት ግንዛቤ ሲኖረን በሥርዓተ ትምህርቱ ውስጥ የሕጻናት ተሳትፎ ምን መሆን እንዳለበት መረዳት እንችላለን፡፡ ለምሳሌ ሕጻኑ ለጨዋታ የሚጠቀምበትን የሸክላ አፈር ወይም ጭቃ በምሳሌነት እንውሰድ፡፡ ቀደም ሲል በሸክላ አፈር ወይም በጭቃ የመጫወት እድል አግኝቶ የማያውቅ ሕጻን ከጭቃው ወይም ከሸክላው አፈር ጋር የሚገናኝበትን መንገድ ይፈልጋል፡፡ የሸክላ አፈሩን ወይም ጭቃውን ይነካል፣ ይወቅጣል፣ ይወጋል፣ ይበሳል፣ ይደነቁላል፣ ያሸታል…ወ.ዘ.ተ፡፡ ጭቃው ምን እንደሆነና አገልግሎቱም ምን ሊሆን እንደሚችል ለማወቅ ይፈትጋል፣ ይፈቀፍቃል፣ ይጨብጣል ወይም ይጠፈጥፋል፡፡ ቀጥሎ ጭቃ ጠቅልሎና በመቆራረጥ/ በማድቦልቦል/ በመጠፍጠፍ ኳስ ወይም እባብ መሳይ ቅርፆች መስራት ይጀምራል፡፡ ቁሶችን ሲያውቅ ከልምድ ያገኛቸውን ዘዴዎች በማቀናጀት ተጨማሪ ቅርፆች ይሰራል፡፡ ፈጠራ ሥራውን እንዳጠናቀቀ ውጤቱን ያስተውላል፡፡ ውጤቱ ሌላ ነገር የሚያስታውሰው ከሆነ ወዲያው ስም ያወጣለታል፡፡ “ተመልከት! ኳስ ሠራሁ” በማለት ውጤቱን ያበስራል፡፡ በፈጠራ ሂደት ወቅት የሚያገኘው ውጤት ሌላ ነገር ባስታወሰው ቁጥር ስያሜውን ለበርካታ ጊዜ ሊለዋውጠው ይችላል፡፡ ይሁን እንጂ ሕጻኑ ከፍ እያለና ትንሽ እየበሰለ ሲመጣ ሊሠራ ያሰበውን በቅድሚያ ይወስናል፡፡
መልካም፣ መልካሙን ለሕፃናት!!
ሣህሉ ባዬ ዓለሙ
Comments