የሕጻናት አጸደ ሕጻናት እድሜ
ሕጻናት ወደ አጸደ ሕጻናት የሚሄዱበት እድሜ እንደሚኖሩበት አካባቢ ቢለያይም በሁለት ዓመታቸው አዳዲስ ነገሮች መማርና ነገሮችን ማስተዋል ይጀምራሉ፡፡ ለአካላዊ እንቅስቃሴ የሚረዷቸውን መራመድ፣ መሮጥና መንጠላጠል ይጀምራሉ፡፡ እንዲህ፣ እንዲህ እያሉም ወደ ሦሰተኛ ዓመት ይሸጋገራሉ፡፡
በሦስት ዓመት እድሜ መሠረታዊ የመናገር ክሂሎት ስለሚኖራቸው የቃላት ክምችታቸው ይጨምራል፡፡ በዙሪያቸው ካሉ ሰዎችና ቢጤዎቻቸው ጋር መግባባት ይማራሉ፡፡ ነገሮችን ይፈትሻሉ፣ ይሞክራሉ፣ ይቀምሳሉ…..ወ.ዘ.ተ፡፡ አንዳንድ ሰዎች ይህን እድሜ “የመገስገስ” እድሜ ይሉታል፡፡ በእርግጥ ይህ እድሜ ሕጻናት የመስማት፣ የመናገር፤ የማስተዋል፣ የመተባበር፣ የመረዳዳትና የእኔነት ስሜትን ማዳበር የሚጀምሩበት እድሜ ነው፡፡ በነፃነት መንቀሳቀስ ስለሚፈልጉ አንዳንዴ የአዋቂዎችን እርዳታ ተስፋ በሚያስቆርጥ ሁኔታ ይቃወማሉ፡፡ ወደ አራተኛ ዓመት መሸጋገሪያ ወቅት ላይ ከገደበ የመውጣት አዝማሚያ ይስተዋልባቸዋል፡፡ አራተኛ ዓመት ላይ “አይሆንም/አይደለም” የሚባሉ የእምቢተኝነት ቃላት ወደ “አዎ/አቤት/እሺ” ወደሚባሉ ገምቢ ቃላት ይቀየራሉ፡፡ በዚህ እድሜ ከየትኛውም ጊዜ በተሻለ ሁኔታ እራሳቸውን የመቆጣጠር፣ የመስጠትና የመቀበል፣ ድርሻን የመውሰድ፣ የመጋራትና የሌላውን ስሜት የመካፈል ባህርያት ማሳየት ይጀምራሉ፡፡ አሁን ከሌሎች ሕጻናት ጋር የመጫወት ፍላጐታቸውና ችሎታ እያደገና እየጨመረ መጥቷል፡፡ በቀጣዮቹ ዓመታት ሕጻናት በፍጥነት ተለዋዋጭ ለሆነው የዕድገት ሂደት ለውጦች ተገዢ በመሆን ወላጆችና መምህራንን ለማስደሰት የሚችሉትን ሁሉ ለማድረግ ይሞክራሉ፡፡ “እደግ“፣ “ተመንደግ፣ “ተማር ልጄ” የሚያሰኝ ወሳኝ የእድሜ ክልል ስለሆነ ውጤቱ ያማረ እንዲሆን ትኩረት እናድርግ"።!
መልካም፣ መልካሙን ለሕፃናት!!
ሣህሉ ባዬ ዓለሙ
Email: sahilubaye@gmail.comand/or ecd@ethionet.et
Comments